ኢትዮጵያ ለ5ኛ ጊዜ በወንዶች የኦሎምፒክ ማራቶን የወርቅ ሜዳል ባለቤት ሆነች

ቻይና 39 ወርቅ ሜዳል በማግኘት ዩናይትድ ስቴትስን በአንድ ወርቅ ብልጫ በመቅደም የአንደኛነት ደረጃን ይዛለች፤ ኢትዮጵያ በታምራት ቶላ የወርቅ ሜዳል አሸናፊነት ከ184 ተወዳዳሪ ሀገራት 49ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች።

Tamirat Tola Paris.png

Tamirat Tola of Ethiopia won the Men's Marathon on day fifteen of the Olympic Games Paris 2024 at Esplanade Des Invalides on August 10, 2024, in Paris, France (L). Gold medalist Tamirat Tola of Team Ethiopia poses on the podium during the Athletics medal ceremony after the Men's Marathon on Day fifteen of the Olympic Games Paris 2024 at Esplanade Des Invalides on August 10, 2024, in Paris, France (R). Credit: Steve Christo - Corbis/Corbis and Michael Steele/via Getty Images

በ2024 የፓሪስ ኦሎምፒክ የወንዶች ማራቶን ውድድር አትሌት ታምራት ቶላ ነሐሴ 4 / ኦገስት 10 በተካሔደው ውድድር 2 ሰዓት ከ 06 ደቂቃ 26 ሰከንድ በመጨረስ የኦሎምፒክ ሬኮርድ ሰብሮ ለወርቅ ሜዳል ባለቤትነት በቅቷል።

የቤልጂየሙ ባሺር አብዲ የብር፣ ኬንያዊው ቤንሰን ኪፕሩቶ የነሐስ ሜዳል ለማሸነፍ በቅተዋል።

በዕለቱ የወንዶች ማራቶን ተወዳዳሪ የነበረው አንጋፋው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ 39ኛ ሆኖ ውድድሩን አጠናቅቋል።

ለማራቶን ውድድሩ ተሰላፊ ሳይሆን ተጠባባቂ የነበረው ታምራት ቶላ የኦሎምፒክ ሬኮርድ ሰብሮ ለወርቅ ሜዳል ባለቤትነት የበቃው በጉዳት ሳቢያ ከውድድሩ የተገለለውን ሲሳይ ለማን ተክቶ ነው።

የ32 ዓመቱ ታምራት ቀደም ሲል ባካሔዳቸው ውድድሮች፤ በሪዮ ኦሎምፒክ በ10 ሺህ ሜትር፣ በ2022 ዓለም አቀፍ ማራቶንና በ2023 የኒውዮርክ ማራቶን በተከታታይ የነሐስ ሜዳሎችን ለኢትዮጵያ ያስገኘ አትሌት ነው።

ታምራት በማራቶን ያስገኘው የወርቅ ሜዳል ኢትዮጵያን በፅጌ ዱጉማ በሴቶች 800 ሜትርና በበሪሁን አረጋዊ የወንዶች 10 ሺህ ሜትር ባገኘቻቸው የብር ሜዳሎች ከ184 ተወዳዳሪ ሀገራት ከነበረችበት 68ኛ ደረጃ ወደ 49ኛ ደረጃ ከፍ ለማለት በቅታለች።

ኢትዮጵያ ቀደም ባሉት አራት የኦሎምፒክ ውድድሮች ዘወትር በሚታወሱት አትሌቶቿ የወርቅ ሜዳሎችን አግኝታለች።

  • አበበ ቢቂላ፤ በ1960 የሮም ኦሎምፒክ ወርቅ
  • አበበ ቢቂላ፤ በ1964 የቶኪዮ ኦሎምፒክ ወርቅ
  • ማሞ ወልዴ፤ በ1968 የሜክሲኮ ከተማ ኦሎምፒክ ወርቅ
  • ገዛኸኝ አበራ፤ በ2000 የሲድኒ ኦሎምፒክ ወርቅ ሜዳሎችን ለሀገራቸው ኢትዮጵያ አስገኝተዋል።
በፓሪስ ኦሎምፒክ 15ኛ የውድድር ዕለት ድረስ በ32 የስፖርት ዘርፎች በተካሔዱ ውድድሮች ቻይናና ዩናይትድ ስቴትስ የሜዳል ሠንጠረዥ ላይ አንደኛና ሁለተኛ በመሆን እየተፈራረቁ ደረጃዎቻቸውን ይዘው አሉ፤

  • ቻይና፤ 39 ወርቅ 27 ብር 24 ነሐስ በድምሩ 90 ሜዳሎችን በማግኘት 1ኛ
  • ዩናይትድ ስቴትስ፤ 38 ወርቅ 42 ብር 42 ነሐስ በድምሩ 122 ሜዳሎችን በማግኘት 2ኛ
  • አውስትራሊያ፤ 18 ወርቅ 18 ብር 14 ነሐስ በድምሩ 50 ሜዳሎችን በማግኘት 3ኛ
  • ኢትዮጵያ 1 ወርቅ 2 ብር በድምሩ 3 ሜዳሎችን በማግኘት 49ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ።

Share
Published 11 August 2024 3:42pm
Updated 11 August 2024 8:32pm
By Kassahun Seboqa Negewo
Source: SBS

Share this with family and friends